ጸሎት አስተምረን -- ወደ ፈተና አታግባን (ክፍል አስራ-አራት)
- Redeatu G. Kassa
- Dec 17, 2017
- 2 min read
“እርሱም በአንድ ስፍራ ይጸልይ ነበር፥ በጨረሰም ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ፦ ጌታ ሆይ... እንጸልይ ዘንድ አስተምረን አለው። አላቸውም፦ ስትጸልዩ እንዲህ በሉ፦ በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ... ወደ ፈተና አታግባን።” (ሉቃ. 11፡4)
ጌታችን ባስተማረን ጸሎት ውስጥ አንዱ የምናቀርበው ልመና እግዚአብሔርን ሆይ ወደ ፈተና አታግባን የሚል ነው። በዚህ አውድ ውስጥ “ፈተና” ተብሎ የተገለጸው ሃሳብ በእንግሊዘኛ “temptation” የተባለው ሃሳብ ነው። ይህም ወደ ኃጢያት የሚመራ ፍላጎት ነው። ሐዋሪያው ያዕቆብ እንደሚያስተምረን የምንፈተነው በገዛ ምኞታችን ስንሳብና ስንታለል ነው። (ያዕ. 1፡14) ከዚያም በኋላ ምኞት ጸንሳ ኃጢያትን ትወልዳለች። የኃጥያትም ፍሬ ወይንም ውጤት ሞት ነው። (ቁ. 15) የውድቀትን ሰንሰለት ስንመለክት ጅማሬው በምኞት ተስቦ መታለልና መፈተን ነው። ፈተናው ካልጨነገፈ ወደ ኃጢያት ያመራል። ኃጢያት ደግም ሞትን መውለዱ የማይቀር ነው። በውድቀታችንም የሆነው ይኼው ነው። በመጀምሪያ ሰው በሰይጣን ማታለል ተስቦ ተፈተነ። ከዚያም ተፈተነ። ፈተናውንም ማለፍ ተስኖት በኃጢያት ወደቀ። ኃጢያትም የዘላለምን ሞት አመጣብን።
ስለዚህ ጉዳይ ጌታችን በሌሎች ስፍራዎችም ከጸሎት ጋር አገናኝቶ ሐዋሪያቱን አስተምሯል። ለምሳሌ በማቴዎስ 26፡41 ላይ “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ” ብሏል። እንዲሁም በማርቆስ 14፡38 ላይ “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉ ጸልዩም” ብሏል። ከነዚህ ክፍሎች የምረዳው ሃሳብ ወደ ፈተና እንዳንገባ በጌታ ፊት ጸጋን መጠየቅ እንዳለብን ነው። በእግዚአብሔር ፊት መጸለይ በእግዚአብሔር ሃሳብ ውስጥ እንድንኖርና ወደ ፈተናም እንዳንገባ ጸጋን ያበዛልናል። እናስታውስ “ወደ ፈተና አታግባን” ብለን ስንጸልይ እግዚአብሔር እርሱ ራሱ የፈተናችን ምንጭ እንደሆነ ማለታችን ሳይሆን እርሱ ወደ ፈተና እንገባ ዘንድ እንዳይተወን (ጥበቃውን ከኛ እንዳያነሳ) መጸለያችን ነው። የፈተና ምንጭ የራሳችን ክፉ ምኞት እንጂ እግዚአብሔር አይደለም። ስለዚህም ሐዋሪያው ያዕቆብ እንዲህ ይመክረናል። “ማንም ሲፈተን፦ በእግዚአብሔር እፈተናለሁ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም።” (ያዕ. 1፡13)
ከዚህ ጸሎት አንጻር አንድ ተጨማሪ ሃሳብ መረዳት አለብን። ጸሎቱ መከራ ከምንለው የፈተና አይነት (trial or suffering) ጋር የተገናኘ አይደለም። ክርስቲያኖች እምነታችን ሊፈተን ይችላል። በእምነታችን መፈተን ሲገጥመን እንደ ሙሉ ደስታ መቁጠር እንዳለብን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል። ይህ ደግም በፈተና አልፈን እንድንጠነክር የሚያደርገን ነው። (1 ጴጥ. 6-7፤ ያዕ. 2- 3) ነገር ግን በአባትያችን ሆይ ጸሎት “ወደ ፈተና አታግባን” ብለን ስንጸልይ የምንጠይቀው በክፉ ምኞት አጥምዶ ወደ ኃጢያት ከሚወስደው ፈተና እግዚአብሔር እንዲጠብቀን ነው። የጸሎቱ ሃሳብ ጸጋን ማለትም የእግዚአብሔርን ጥበቃ መጠየቅ ነው። አባታችን ሆይ ወደ ፈተና አታግባን። አሜን!
Recent Posts
See All“ተስፋን ቃል የሰጠዉ የታመነ ነዉና እንዳይነቃነቅ የተስፋችንን ምስክርነት እንጠብቅ። (ዕብ 10፡ 23) ተስፋ ሰው በሕይወቱ እንደሚሆን በእርግጠኝነት የሚጠብቀው ነገር ነው። እያንዳንዱ ሰዉ ተስፋ የሚያደርገዉ...
ባለንበት ጊዜ በተለይም በ COVID 19 ወረርሽኝ የተነሳ በአብዛኛው ቤት ውስጥ ተከተን ባለንበት በዚህ ወቅት፤ የተለያየ ድምጽ፣ አስተሳሰብ፣ ጩኸት፣ አመለካከት እና ፕሮፓጋንዳ የምንሰማበት አጋጣሚ ሰፊ ነው። በተለይም...
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለይም በምእራቡ አለምና በሃገራችን በኢትዮጲያ በተወሰነ መልኩ በትምህርት ቤቶች፣ በአንዳንድ ቢሮዎች፣ በቤትና በአፓርትመንት መስኮቶች ላይ በወረቀት የተቀለመ ህብረቀለማትን አዋህዶ የያዘ...
Comments