ምስክሮች
በፈለገ-አብርሃም ለጥሪው ልታዘዝ፣ በስራ ሚገለጥ የምነትን ፅድቅ ልያዝ፣
በመንፈሱ እንዳየ ከሞተ ኣካል ህይወት፣
ያስነሳዋል እንዲል ልጅ አቅርቦ መስዋኢት፣
እኔም ድልን ላብስር ትንሳኤውን ላሽትት።
የልብ ብርህን ስጠኝ እንደ ባርያህ ሙሴ፣
ከግብፅ ተድላ ይልቅ እንድትሻህ ነፍሴ፣
ለም ዝና ሚያስንቅ ክብርህን አይቼ፣
ጉልበቴ ሳይደክም ሳይፈዙ አይኖቼ፣
በከፍታ ልሙት ተራራ ወጥቼ።
እግሬ ዘይት ይጥለቅ በአሴር ምሳሌ፣
እድሜዬም ሲጨምር እንዲታደስ ሃይሌ፣
ይሞላ ጏዳዬ በሚተርፍ በረከት፣ ቀባኝ በመንፈስህ አጫማኝ በብረት፣
ጠላቶቼን ላድቅቅ በስምህ ሃይል ጉልበት።
ታምነው እንደሄዱት ካሌብና ኢያሱ፣
ባንተ አይን ልያቸው ጥላቶቼ ይነሱ፣
እንደ ተናገረኝ እንደሁ ይሆናል፣ ብዬ ልሰማራ አንግቤ የተስፋ ቃል፣
ተራራውን ልውረስ አስለቅቄ በኃይል።
ባንተ ደስ ይበለኝ እንደ ልብህ ዳዊት፣
ሳልቆጥብ ላምልክህ በፊትህ ልጫወት፣
በስምህ ወንጭፌ ጎልያድን ልጣል ላስወግድ ተግዳሮት፣
በትውልዱ መሃል እዳገለገለህ በሃሳብህ ቅኝት፣
ለኔም ክብሬ ይሁን በዘመኔ መሮጥ መፈለግ ያንተን ፊት።
ለጳውሎስ ያበራው የክብርህ ብርሃን፣
አብዝቶ ይክፈተው የኔንም የውስጥ አይን፣
ምልክትን ልፍጠን ልዘርጋ ወደ ፊት፣
ተጋድሎዬ ይላቅ በሚጨምር ቅባት፣
የማዳኑን ወንጌል ላብስር ለፍጥረታት።
እኔም እንደ ማርያም እንደ መቅደላዊት፣
በእግሮችህ ስር ልረፍ ልቀመጥ ለመስማት፣
እግርህ ላይ ላፍስሰው ሽቶዬን ሰብሬ፣
በፀጉሬም ላብሰው ትስገድልህ ክብሬ፣
ባንተ ምህረት ነው በህይወት መኖሬ።
ጥቂት እናንሳ እንጂ እንዲሆኑን አብነት፣
የኃይሉን ብርታት የቀመሱ ድል የነሱ በእምነት፣
ደግሞም የሚበልጠውን ክብር አይተው፣
አምነው የሞቱ ስለ እምነትም የተሰው፣ እንደ ደመና የከበቡን የሚያበረታን ፈለጋቸው፣
ቀድመውን የጨረሱ ምስክሮቹ ብዙ ናቸው።
ደግሞ አለ በፊቱ ስላለው ደስታ ነውርን ንቆ በመስቀል የታገሰ፣ አዲስ መንገድ ጠርጎ በፊታችን የሄደ ሩጫውን የጨረሰ፣
ምት ሊይዘው ያልቻለ አሸንፎ በህይወት የነገሰ፣ የድላችን ብስራት የእምነታችን እራስ፣ ሊቀ ካህናችን ቀዳሚው ኢየሱስ።
የምስክሮቹን ፋና ተከትለን ይልቁንም እያየን ጌታችንን፣ ቶሎም የሚከበንን ሃጥያት አስወግደን ሸክምን ሁሉ ጥለን፣
ከዝለትና ከእንቅልፍ ከመታከትም ወጥተን፣ ቀንዲላችንን ዘይት ምልተን ኃይላችንም እንደ ንስር አድሰን፣ በተጨመረልን እድሜ በተሰጠን አዲስ አመት፣ እንገስግስ ወደፊት ሩጫችንን እንሩጥ በትግስት።