top of page

ኢያሱ -- እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር የሆነ አገልጋይ

“በሕይወትህ ዕድሜ ሁሉ ማንም አይቋቋምህም፤ ከሙሴ ጋር እንደ ሆንሁ እንዲሁ

ከአንተ ጋር እሆናለሁ፤ አልጥልህም፥ አልተውህም...በምትሄድበት ሁሉ አምላክህ እግዚአብሔር

ከአንተ ጋር ነውና ጽና፥ አይዞህ አትፍራ፥ አትደንግጥ ብዬ አላዘዝሁህምን?” (ኢያሱ 1፡ 5,9)

ኢያሱ ሁልጊዜ እግዚአብሔርን የሚፈልግ አገልጋይ ነበር። ሁልጊዜ የእግዚአብሔር

ክብርና መገኘት ካለበት ከመገናኛው ድንኳን አይለይም። እርሱ እግዚአብሔርን ይፈልግ የነበረው

ለጉዳዩ ብቻ ሳይሆን ለሕይወት ነበር። አስቀድም እግዚአብሔርን ይፈልጋል። ከዚህም የተነሳ

በሚሰራው ስራ ሁሉ የተከናወነ አገልጋይ ነው።

እንዲሁም ደግሞ እያሱ እግዚአብሔርን በፈለገው መጠን እግዚአብሔር የተገኘለት

አገልጋይ ነው። ግዚአብሔር ለሚፈልጉት ይገኛል። በጸሎት ወደ እርሱ ስንቀርብ ይሰማናል።

ለዚህም ነው በኤርሚያስ 33:3 ላይ ቃሉ “ወደ እኔ ጩኽ፥ እኔም እመልስልሃለሁ፤ አንተም

የማታውቀውን ታላቅና ኃይለኛ ነገርን አሳይሃለሁ” የሚለን። እግዚአብሔርን ፈልጎ ያፈረ የለም።

እግዚአብሔርን የሚፈልግ ይጸናል። (መዝ. 105:4) እግዚአብሔርን የሚፈልግ በሕይወት ይኖራል።

(አሞጽ 5:6) እግዚአብሔርን የሚፈልግ ምህረትን ይቀበላል። (ሰፎ. 2:3) እግዚአብሔርን

የሚፈልግ ልብ ደስ ይለዋል። (መዝ. 16:10) እግዚአብሔርን የሚፈልግ ለኑሮ የሚያስፈልገው ሁሉ

ይጨመርለታል። (ማቴ. 6:33)

ኢያሱ እግዚአብሔርን በፈለገው መጠን እርሱ ደግሞ “ከአንተ ጋር አለሁ” ብሎታል።

ከሙሴ ሞት በኋላ ህዝቡን ወደ ርስታቸው የማግባት ታላቅ ኃላፊነት የተቀበለው ኢያሱ ከተሰጠው

ጥሪና አገግልግሎት ጋር የእግዚአብሔር አብሮነት ተስፋ የተሰጠው አገልጋይ ነው። እግዚአብሔር

እራሱ በቃሉ “ከሙሴ ጋር እንደ ሆንሁ እንዲሁ ከአንተ ጋር እሆናለሁ” አለው። በሚሄድበትም

ሁሉ አምላኩ እግዚአብሔር ከርሱ ጋር እንደሚወጣ ቃልን ተቀበለ። ኢያሱ ለተሰጠው ታላላቅ

የድል ተስፋዎችና የመጽናቱ ምክንያት እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር መሆኑ ነው። በሕይወት ዘመንህ

የሚቋቋምህ የለም የተባለው እግዚአብሔር ከርሱ ጋር ስለሆነ ነው። ጽና፣ እይዞህ፣ አትፍራ፣

አትደንግጥ የሚለውን ትእዛዝ የተቀበለው ከእግዚአብሔር አብሮነት ተስፋ ጋር ነው።

ለኢያሱ በእስራኤል ሕዝብ ፊት ሞገስ የሆነለት የእግዚአብሔር ከርሱ ጋር መሆን ነው።

ኢያሱ ሕዝቡን በተናገረ ጊዜ ሕዝቡ አንድ ነገር ብቻ ነበር ያሉት፡ “ያዘዝኸንን ነገር ሁሉ እናደርጋለን

ወደምትልከንም ስፍራ እንሄዳለን። በሁሉም ለሙሴ እንደ ታዘዝን እንዲሁ ለአንተ ደግሞ

እንታዘዛለን፤ ብቻ አምላክህ እግዚአብሔር ከሙሴ ጋር እንደ ነበረ ከአንተ ጋር ይሁን።” (ኢያ. 1:16)

ወገኖቼ፦ እኛም በአዲስ ኪዳን የተቀበልነው ትልቁ ተስፋ አማኑኤል ነው። አማኑኤል

ማለት እግዚአብሔር ከኛ ጋር ማለት ነው። የእግዚአብሔር ልጅ ጸጋን እና እውነትን ተሞልቶ

በህዝቡ መካከል አድሯል። እንኪያስ እግዚአብሔር ከኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል?

እግዚአብሔር ከኛ ጋር ከሆነ ማን ይቋቋመናል? ከእግዚአብሔር ጋር የሚጣላ ይደቅቃል።

የመውጊያውን ብረት ለሚቃወም ለእርሱ ይብስበታል።


Recent Posts
Archive
Search By Tags
No tags yet.
Follow Us
  • Facebook Basic Square
  • Twitter Basic Square
  • Google+ Basic Square
bottom of page